ከሦስት ሳምንታት በፊት አደጋ ስለደረሰበት የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላንን የተመለከቱ ዝርዝር መረጃዎች እየወጡ ነው።
በዚህም በቦይንግ 737 ማክስ ላይ ያለው አውሮፕላኑ ዝግ እንዳይል ወይም እንዳይቆም የሚያደርገው የአውሮፕላኑ ሥርዓት የ157 ሰዎችን ህይወት ለቀጠፈው አደጋ ምክንያት እንደሆነ እየተነገረ ነው።
አደጋው ከመድረሱ በፊት በሁለቱ አብራሪዎች መካከል የተደረገን ምልልስ ጠቅሶ ዎል ስትሪት ጆርናል እንደዘገበው፤ የአውሮፕላኑ የሬዲዮ ግንኙነት ከመቋረጡ በፊት አንደኛው አብራሪ "ቀና አድርገው! ቀና አድርገው!" በማለት ለባልደረባው ሲናገር ተሰምቷል።
በአውሮፕላኑ ላይ ያጋጠመውን ችግር ለመቆጣጠር ያስችላል የተባለውን ሥርዓት አብራሪዎቹ ቢጠቀሙም አደጋውን ለማስቀረት እንዳልተቻለ እየተደረገ ላለው ምርመራው ቅርብ የሆኑ ምንጮች ለጋዜጣው ተናግረዋል።
አደጋ ከደረሰበት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይን 737 ማክስ አውሮፕላን የበረራ መረጃ መሰብሰቢያ ሳጥን ውስጥ ከተገኘ የመጀመሪያ ደረጃ መረጃ መሰረት አደጋው ከመድረሱ በፊት እያሽቆለቆለ ያለውን አውሮፕላን ሊታደግ ይችላል የተባለው የአውሮፕላኑ ሥርዓት እንዲሰራ ተደርጎ እንደነበር አመልክቷል።
ዘ ዎል ስትሪት ጆርናል የተባለው ጋዜጣ ስለአደጋው የመጀመሪያ ደረጃ ውጤት ስማቸው ያልተጠቀሱ ምንጮችን ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው የአውሮፕላኑ ከፍታና ዝቅታ ለመቆጣጠር እንዲያስችል ተደርጎ የተሰራው የኮምፒውተር ሥርዓት ችግር እንዳለው አመልክቷል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን የበረራ ቁጥር ኢቲ302 መጋቢት 1/2011 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ጠዋት 2፡38 በመነሳት ሁለት ሰዓት ብቻ ለሚፈጀው በረራ ወደ ናይሮቢ ፊቱን ቢያዞርም ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ችግር ገጥሞታል።
አውሮፕላኑ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ከተነሳ ከስድስት ደቂቃዎች በኋላም 48 ኪሎሜትሮችን ከአዲስ አበባ በስተደቡብ ምሥራቅ ተጉዞ ከቢሾፍቱ አቅራቢያ ባለችው ቱሉ ፈራ መንደር ውስጥ ነበር ወድቆ የተከሰከሰው።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአውሮፕላኑ ዋና አብራሪ ያሬድ ጌታቸው ችሎታን በተመለከተ አብራሪው ከ8ሺህ ሰዓታት በላይ የማብረር ልምድ እንዳለው በመጥቀስ "የሚያስመሰግን ብቃት" አለው ብሏል።
አደጋው በደረሰበት ዕለትም አብራሪው ያሬድ ጌታቸው ችግር እንደገጠመውና ተመልሶ ለማረፍ ለበረራ ተቆጣጣሪዎች መልዕክት አስተላልፎ ነበር።
ከዚህ አደጋ ጋር በተያያዘ የአውሮፕላኑ የደህንነት መጠበቂያ ሥርዓት ለሚደረገው ምርምራ ዋነኛው ጉዳይ ሆኗል
Image copyrighከዚህ አደጋ ጋር በተያያዘ የአውሮፕላኑ የደህንነት መጠበቂያ ሥርዓት ለሚደረገው ምርምራ ዋነኛው ጉዳይ ሆኗል።
ኤምካስ የተባለውና አውሮፕላኑን በከፍተኛ ሁኔታ ወደላይ እንዳይወጣ ወይም ወደታች እንዳያሽቆለቁል ለመቆጣጠር እንዲቻል ተብሎ የተሰራ ሥርዓት ነው።
በአውሮፕላኑ ዝግ ሲል በትክክለኛው አቅጣጫ እንዲበር ለማስቻል የሚፈለገውን ኃይል ለማግኘት ወደ ላይ ወይም ቁልቁል በመሄድ ወደሚፈለገው ከፍታ ይመለሳል። ይህ ሳይሆን ከቀረ ግን በአውሮፕላኑ ክንፎች በኩል ያለውን የመቆጣጠሪያ አቅም በመቀነስ አውሮፕላኑ እንዲወድቅ ሊያደርገው ይችላል።
በተለመደው ሁኔታ አውሮፕላኑን ከዝግታ ለማውጣት አብራሪው የአውሮፕላኑ አፍንጫ ወደታች እንዲያዘቀዝቅ ያደርጋል። አደጋው በደረሰበት ቦይንግ 737 ማክስ አይነት አውሮፕላኖች ላይ ያለው የመቆጣጠሪያ ሥርዓት (ኤምካስ) ግን እንዲህ አይነቱ ሁኔታ ሲከሰት አውሮፕላኑን እራሱ አስተካክሎ ወደ ትክክለኛው ቦታ ይመልሰዋል።
አውሮፕላኑ ላይ ተመሳሳይ ነገር የሚከሰት ከሆነና ኮምፒውተሩ ይህንኑ ካወቀ የመቆጣጠሪያ ሥርዓቱ በተደጋጋሚ የማስተካከያ እርምጃን በእራሱ ይወስዳል።
በኢትዮጵያው አየር መንገድ ላይ አደጋው ከመድረሱ አምስት ወራት ቀደም ብሎ ተመሳሳይ አደጋ የደረሰበት የኢንዶኔዢያው አውሮፕላንም የበረራውን ማዕዘን በሚያሰላው የአውሮፕላኑ መቆጣጠሪያ ላይ ተመሳሳይ አይነት እክል ገጥሞት እንደነበር ተገልጿል።
በቦይንግ ምስለ በረራ ላይ በተደረገ ሙከራ እንደተረጋገጠው ኤምካስ የተባለው መቆጣጠሪያ ከሚጠበቀው በላይ ከበድ ያለ በመሆኑ በተደጋጋሚ የአውሮፕላኑ አፍንጫ ቁልቁል እንዲያዘቀዝቅ ያስገድዳል።
በኢንዶኔዢያው አውሮፕላን ላይ የደረሰውን አደጋ ለማወቅ በተደረገው የምስለ በረራ ሙከራ ላይ እንደተደረሰበት አውሮፕላኑ ቁልቁል በአፍንጫው ባህር ላይ ሊከሰከስ መሆኑን ያወቁት ከ40 ሰከንዶች ያነሰ ጊዜ ሲቀራቸው መሆኑን ኒውዮርክ ታይምስ ዘግቧል።
ይህንንም ተከትሎ ቦይንግ ኤምካስን እንዴት መጠቀም እንደሚቻል ለአብራሪዎች መመሪያ ቢያወጣም፤ ነገር ግን በአውሮፕላኑ ላይ ያለውን ሥርዓት የሚቆጣጠረው ሶፍትዌር ላይ ያስፈልግ የነበረው መሻሻያ ዘግይቶ ባለፈው ሳምንት ነው ይፋ የተደረገው።
በተጨማሪም በበረራ ወቅት ችግር በሚያጋጥም ጊዜ አብራሪዎችን ሊያስጠነቅቅ ይችል የነበረው የማስጠንቀቂያ መብራትም አደጋው በደረሰባቸው ሁለቱ የኢትዮጵያ እና የኢንዶኔዢያ አውሮፕላኖች ላይ አልተገጠመም ነበር።
ከሁለቱ አደጋው ከደረሰባቸው አውሮፕላኖች የተገኙ የበረራ መረጃዎች ተመሳሳይነት እንዳላቸው መርማሪዎች አመልክተዋል።
የአውሮፕላኖቹን ወደ ላይ የመውጣትና የመውረድ ፍጥነት ንባብ እንደሚያመለክተው ሁለቱም አውሮፕላኖች ከፍና ዝቅ እያሉ እንደነበሩና አብራሪዎቹም ይህንን በመቆጣጠር አውሮፕላኖቹ ከፍ ብለው እንዲበሩ ጥረት ሲያደርጉ ነበር።
ከኢትዮጵያ ብሔራዊ የትራንስፖርት ደህንነት ቦርድ ጋር በመሆን ምርመራውን እያካሄደ የሚገኘው የአሜሪካ የአየር ትራንስፖርት ባለስልጣን እንዳለው ከአደጋው ስፍራና ከሳተላይት የተገኙ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ሁለቱ አውሮፕላኖች ላይ በጣም የሚመሳሰሉ ነገሮች እንደታዩ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን የበረራ መረጃ መመዝገቢያውና የአብራሪዎቹ ክፍል ድምጽ መቅጃው ወደ ፈረንሳይ ተወስዶ ምርመራ ተደርጎበታል።
ምንጭ .bbc